Saturday, March 28, 2020

የቤተ ክርስቲያን ሁሉን አቀፍ ጸሎት/Church's Prayer for All

Corona Virus/ኮሮና ቫይረስ

Corona Virus/ኮሮና ቫይረስ 


Corona Virus/ኮሮና ቫይረስ ስያሜ የመተላለፊያ መንገዶች፣ መከላከያ እና ማብራርያ


ሰላም ጤና ይስጥልኝ ከአውደ ጥናት ነው። ምሕረትና ቸርነት የባሕርዩ የሆነ ልዑል አምላክ በቸርነቱ ብቻ በሕይወት ጠብቆ ለዚች ቅጽበት ስላደረሰን የተመሰገነ ይሁን፤ አሁንም በማይለካው ፍቅሩ የተለመደውን ቸርነቱን አይንፈገን። ስለ እናቱ ስለ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያምና ስለ ወዳጆቹ ቅዱሳን ሁሉ ብሎ እንደ በደላችን አይቁጠርብን።

ዛሬ  ይህንን ቪዲዮ ያዘጋጀሁት ዓለምን ከዳር እስከዳር ስለ ተቆጣጠረው፤ ሰብአዊ ፍጡርን ሁሉ ስላስጨነቀውና ግራ ስላጋባው ተላላፊ ወይም ወረርሽኝ በሽታ የጤና ባለሙያዎች የሚናገሩትን በመተርጎም በተቻለኝ መጠን ግልጽና ቀላል በሆነ አማርኛ ለናንተ መረጃ ለመስጠት ነው። ይህ መረጃ የጤና ባለሙያዎች እና የአካባቢያችሁ ባለሥልጣናት ከሚሰጧችሁ መረጃ ጋር ተጨማሪ ሆኖ ሊረዳችሁ፤ ከዚህ በፊት የሰማችሁትን መረጃም  ሊያስታውሳችሁ የሚችል ነው ብየ አምናለሁ።

መጽሐፉን ለመግዛት ይህንን (ራሱ መጽሐፉን) ይጫኑት



የተላከብን ሕመም አዲስና መድሃኒት የሌለው መሆኑን ሁላችንም ሰምተናል። ስለዚህ መድኃኒታችን መድኃኒት ያልተገኘለትን ዓለም ያዳነው መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ መሆኑን እናምናለን፤ እውነትም ነው።

እግዚአብሔር ራሳችንን የምንጠብቅባቸው መሣሪያዎችን ማለትም እያንዳንዳቸውን የሰውነት ክፍሎቻችንን ሰጥቶናል። ስለዚህ በተቻለ መጠን እርሱ እንድንጠቀምባቸው የሰጠንን መሣሪያዎች እየተጠቀምን ራሳችንን ለመጠበቅ መዘጋጀትና ከአቅም በላይ የሆነብንን ደግሞ ሁሉን ለሚችል ለእርሱ መስጠት ይገባናል። ይህ የትክክለኛ አማኝ ሥራ ነው ብየ አምናለሁ።

እኔ የምሠራበት መሥሪያ ቤት ምድቡ ከጤና ማዕከላት ውስጥ ነው። ከ(CDC) ማለትም ከተላላፊ በሽታወች መቆጣጠሪያ ማዕከላት በጣም የቀረበ ክትትል የሚደረግበት መሥሪያ ቤት ነው። ስለዚህ የተሟላ መረጃ በየቀኑ ይሰጠናል። በመሆኑም እናንተም በተለያዩ መንገዶች መረጃውን የምታገኙ መሆናችሁን ባውቅም እኔም በበኩሌ የሰማችሁትን በተለያየ አቀራረብና መንገድ ደጋግማችሁ ብትሰሙት ይጠቅማል ብየ በማሰብ ነው። ያቀረብኩላችሁ እንደሚጠቅማችሁም ርግጠኛ ነው። ምክንያቱም መረጃን የመሰለ ነገር የለም ሲደጋገምም የበለጠ በአእምሮ ይቀረጻል እንጂ አይከፋም። እግዚአብሔር ሁላችንንም በቸርነቱ ይጠብቀን።

መጽሐፉን ለመግዛት ይህንን (ራሱ መጽሐፉን) ይጫኑት


በመጀመሪያ ከስያሜው እነሳለሁ
ስሙን “ኮሮና ቫይረስ” ስርጭቱን ደግሞ “ፓን ደሚክ” በማለት ይጠሩታል። የወረርሽኝን ሕመም “ኤፒ ደሚክ” እና “ፓን ደሚክ” በማለት ይጠሩታል። ቃላቱ መሠረታቸው ከግሪክ እና ከላቲን ነው። እኔ ግን የማውቀውን የክሪኩን ትርጉም እናገራለሁ።
ኤፒ-ደሚክ፡ = ባጭሩ ይዘታዊውን ትርጉም ስንናገር “አገር አቀፍ ወረርሺኝ” ልንለው እንችላለን
በአንድ አካባቢ፤ በአንድ አገር በሚኖር ሕብረተ-ሰብ ውስጥ የተከሰተና በፍጥነት የሚዛመት ተላላፊ ወይም ወረርሽኝ “ኤፒ ደሚክ” ይባላል።

የቃላቱን ትንታኔ በተመለከተ “ኤፒ” ማለት በ፤ በላይ፤ በውስጥ ወዘተ ማለት ሲሆን “ደሚክ” ማለት ደግሞ “ዲሞስ” ወይም “ዲሞቲክ” ከሚለው የግሪክ ቃል “ሕዝብ” ወይም “የሕዝብ” ማለት ነው። ስለዚህ “ኤፒ ደሚክ” ማለት በአንድ አካባቢ በሚኖር ብዙ ሕዝብ ላይ በፍጥነት የሚሰራች ወይም የሚዛመት ተሐዋሲ ወይም ወረርሽኝ ማለት ነው። “ተሐዋሲ” የምንለው ቫይረሱን ሲሆን “ወረርሽኝ” ስንል ደግሞ ስርጭቱን ነው።

ፓን ደሚክ፡ ደግሞ = ባጭሩ ይዘታዊውን ትርጉም ስንናገር “ዓለም አቀፍ ወረርሺኝ” ልንለው እንችላለን
የቃላቱ ትንታኔ “ፓን” ማለት በግሪከኛ “ሁሉ”፡ማለት ነው። ለምሳሌ “ፓንዶክራቶስ” “ፓንዶ ዲናሞስ” ማለት ሁሉን የሚገዛ፤ ሁሉን ቻይ ወዘተ ማለት ነው። ስለዚህ “ፓን ደሚክ” ማለት ወይም ይሚባለው በአንድ አገር እና በአንድ አሕጉር ከሚኖር ሕዝብ አልፎ በአብዛኛው የዓለም ክፍል በሚኖር ሕዝብ ላይ በፍጥነት የሚዛመት ተላላፊ ብሽታ ነው።

አንድ ተላላፊ ሕመም ከአንድ አገር አልፎ ወደ ሌላው አገር ሲዛመት ማለትም በዓለም አቀፍ ደረጃ ሲዳረስ ቢያንስ በአብዛኛው ዓለም ሲደርስ ስሙ ከ “ኤፒደሚክ” ወደ  “ፓን ደሚክ” ይቀየራል። ወይም ፓን ደሚክ ተብሎ ይጠራል። በቀላል አማርኛ “ዓለም አቀፍ ወረርሽኝ” ማለት ነው። ይህንን ስያሜ የሚሰጠው የዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ወይም ማዕከል ነው።

ታስታውሱ እንደሆነ ኮሮና ባይረስ ገና በቻይና ሲነሣ በሌሎችም የተወሰኑ አገራት ሲዛመት ስሙ ገና አልተቀየረም ነበር። “ኤፒ ደሚክ” የሚለውን ስም እንደያዘ ነበር። በኋላ ግን በአብዛኛው የዓለም ክፍል ሲሰራጭ “ፓን-ደሚክ” የሚለውን ስያሜ አገኘ።
እስከ አሁን ከዚህ በላይ የተነጋገርነው አንድ ተላላፊ በሽታ አገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ስያሜ እንዴት እንደሚሰጠውና የስያሜው ትርጉም ምን እንደሆነ ነው።

ኮሮና ቫይረስ ምንድን ነው?
ኮሮና ባይረስ ባጭሩ ቅርጹን መሠረት አድርጎ የተሰየመ ሲሆን እንደ አክልል ክብ ስለሆነ ከቅርጹ በመነሳት “ክብ ወይም ዘውድ መሰል ቅርጽ ያለው ተሐዋሲ” ብለውታል ማለት ነው።
እንዴት ይተላለፋል?
በንክኪ እና በተለያየ መንገድ ቫይረሱ ወደ አካላችን ውስጥ ሲገባ ማለትም ከአካላችን ክፍት በሆኑ የአካል ክፍሎች አልፎ ወደ ውስጥ ሲገባ ማለት ነው፤ ለምሳሌ ክፍት የሆኑ የአካላችን ክፍሎች ከሚባሉት ዋና ዋና ዎቹ እና በቀላሉ ሊጋለጡ የሚችሉት “አፍ” አፍንጫ፤ እና “ዓይን” ናቸው። ሌሎችም እንዳሉን አትርሱ።

እንዴንት መከላከል ይቻላል?
ይህንን ቫይረስ ከምንከላከልባቸው መንገዶች ዋና ዋናዎቹ
1.  እጅን ለ20 ሰከንድ በሳሙና በደንብ መታጥብና ከታጠብን በኋላም በንጹህ ሶፍት ወይም ናብኪን ማድረቅ፤ ወይም ውሃ ካላገኘን በአልኮሆል ወይም የእጅ ማጽጃ (ሃንድ ሳኒታይዘር”) በደንብ መጥረግ።

ለምን እንታጠባለን? የእጅ መታጠብ ውጤት
ብዙ ጊዜ የተለያዩ ነገሮችን ስለ ምንነካ ሰዎችን ስለምንጨብጭ ባይረሱ በእጃችን ላይ ይኖራል ወይም ይገኛል ተብሎ ይታመናል፤ ስለዚህ እጃችንን ለ20 ሰከንዶች በሳሙና እና በውሃ በምንታጠብ ጊዜ ወይም በአልኮል በምናጸዳው ጊዜ በእጃችን ላይ የነበረው ባይረስ ወይም ተሐዋሲ ይሞታል፤ ከሞተ ደግሞ ምንም የሚፈጥረው ሕመም አይኖርም።

2.  ከሰዎች ጋር አለመነካካት፡ 
ከሚስሉ እና ከሚያስነጥሱ ሰዎች በ6 ፊት ወይም ስድስት ጫማ ርቀት መሆን፤ ማለትም አለመቅረብ። ሰላምታችን ያለመነካካትና ያለ መቀራረብ በቃል ብቻ መሆን አለበት።

ለምን በርቀት መሆን አስፈለገ? 
ከሚስሉ እና ከሚያስነጥሱ ሰዎች በርቀት መሆን ያስፈለገበት ምክንያት ወይም የሚሰጠው ጥቅም፦ በምንስልና በምናነጥስ ጊዜ አፋችን እና አፍንጫችን ይከፈታል፤
በዚህ ጊዜ ፈሳሾች ከአፋችን እና ከአፍንጫችን ወጥተው በቅርበት ወዳሉ ሰዎች አካል ሊፈናጠሩና ወደ ሌላው ሰው አፍንጫና አፍ ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ፤ የሳለው ወይም ያስነጠሰው ሰው ኮሮና ቫይረስ ያለበት ከሆነ ቫይረሱ በምራቆቹ ወይም በፈሳሾቹ ውስጥ አብሮ አለ። ይህ ከሆነ ደግሞ ቫይረሱ ወደ አካላችን ከምራቆቹ ጋር ገባ ማለት ነው እንታመማለን።

3.  አፍን፤ አፍንጫን እና ዓይንን ባልታጠበ እጅ ከመነካካት መቆጠብ፡

ለምን? ባልታጠበ እጅ ፊትን በተለይ ክፍት የሆኑ አካላቶቻችንን ለምሳሌ አፋችንን፤ አፍንጫችንን፤ እና ዓይናችንን ባልታጠበ እጅ ከመነካካት መቆጠብ በቀላሉ በባይረሱ ከመጠቃት እንድናለን ። ከላይ እንዳየነው እጆቻችን ብዙ ነገሮችን ይነካካሉ ስለዚህ ቫይረሱ ያለበትን ነገር ለምሳሌ መዝጊያ፤ ጠረጴዛ፤ ወንበር ልብስ፤ የመኪና በር፤ ወዘተ ልንነካ እንችላለን፤ በዚህ ጊዜ ቫይረሱ ከነካነው ነገር ወይም አካል ወደ እጆቻችን ይሸጋገራል ማለት ነው።

 ከዚያ በኋላ ሳንታጠብ አፋችንን፤ አፍንጫችንን፤ እና ዓይናችንን ከነካን ቫይረሱን ወደ አካላችን ውስጥ አስገባነው ማለት ነው። ስለዚህ ባልታጠበ እጅ ፊታችንን መደባበስና መንካት የለብንም።


የኮሮና ቫይረስ በሚከተሉት ነገሮች ከፊት ለፊታቸው የተጻፉን የጊዜ ርዝመቶ ሳይሞት በሕይወት መቆየት ይችላል። ስለዚህ የተጠቀሱትን እና ሌሎችንም ነገሮች ከነካን፤ ወይም በተጠቀሱት አካባቢዎች በተጠቀሰው የጊዜ ገደብ ውስጥ ካለፍን ጥንቃቄ ማድረክ አለብን። ካልሆነ ግን ልንጠቃ እንችላለን ማለት ነው።

·         በአየር ላይ፡ = ለ3 (ሦስት) ሰዓታት (አንድ በቫይረሱ የተያዘ ሰው አፉን ሳይዝ ካስነጠሰ በአካባቢው ላይ ለ3 ሰዓታት ስለሚቆይ በዚያ ካለፍን ልንጠቃ እንችላለን (ስካርብ ወይ ሻፕ መልበስ አፍን እና አፍንጫን መሸፈን መልካም ነው)
·        በመዳብ እና መዳብ ነክ ነገሮች፡ = ለ4 (አራት) ሰዓታት
·        በካርቶን እና ካርቶን ነክ ነገሮች፡ = ለ24 (ለሃያ ዐራት) ሰዓታት
·        በብረትና ብረት ነክ ነገሮች፡ = ከ2-3 (ከሁለት እስከ ሦስት) ቀናት
·        በፕላስቲክ እና ፕላስቲክ ነክ ነገሮች፡= ከ2-3 (ከሁለት እስከ ሦስት) ቀናት ሳይሞት መቆየት ይችላል።

ይህ የሚያሳየን የምንነካው ሁሉ ስጋት ያለው ስለሆነ፡   እጃችንን ሳንታጠብ ምግብ አንደማንበላ ሁሉ በተጠቀሰው ዓይነት መንገድ እጆቻችንን ሳንታጠብ ፊታችችንን መንካት የለብንም።

ልዑል አምላክ በቸርነቱ  ይጠብቀን
ከአውደ ጥናት

Sunday, March 22, 2020

በሥጋዊውና በመንፈሳዊውም ሕይወታችን ልንመራባቸው የሚገቡ የሥነ ምግባር ጥቅሶች/Ethical and Moral vers...



በአውደ ጥናት ዘአማርኛ እየተዘጋጁ የሚቀርቡ


በሥጋዊውና በመንፈሳዊውም ሕይወታችን ልንመራባቸው የሚገቡ የሥነ ምግባር ጥቅሶች
በተለይ ለወጣቶችና ለሕጻናት መልካም ሥነ ምግባርን የሚያስተምሩ ጥቅሶች ስለ ሆኑ 

ወላጆች ለልጆቻችሁ እያብራራችሁ ማስተማር አለባችሁ በማለት አሳስባለሁ

“ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ይተዋወቁ” የሚለውና እና “ልሣነ ግእዝ የጋራ ቋንቋችን” ሌሎችንም መጻሕፍቶቼን ከአማዞን ለመግዛት የሚከተለውን ይጫኑ
  https://amzn.to/2WE6B8f https://amzn.to/2xk8mwB